የመጀመሪያው የመዛግብትና የጽሑፍ ቅርሶች ጉባዔ እየተካሄደ ነው

መጻሕፍት ለዕውቀት ገበታ፣ መዛግብትና የጽሑፍ ቅርሶች ለታሪክ ትውስታ በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው የመጀመሪያው የመዛግብትና የጽሑፍ ቅርሶች ጉባዔ እየተካሄደ ነው። የኢትዮጵያ ቤተመዛግብትና ቤተመጻሕፍት አገልግሎት ከደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ከመጋቢት 2-4/2015 ዓ.ም ያዘጋጁት የመጀመሪያው ዙር የመዛግብትና የጽሑፍ ቅርሶች ጉባዔ በደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ በአለቃ ተክሌ ገ/ሀና አዳራሽ እየተካሔደ ይገኛል።
በጉባዔው የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዘዳንት ዶ/ር አነጋግረኝ ጋሻው፣የአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ይኩኖአምላክ መዝገቡ፣የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህል፣ቱሪዝምና ኪነ ጥበባት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ሒሩት ካሳው፣ቀሳውስትና የሐይማኖት አባቶች፣መምህር አገኘሁ አዳነ፣ደራሲ በሁሉም አለበል፣ተጋባዥ ጥናት አቅራቢዎች፣ተማሪዎችና ከአገልግሎቱ የሚመለከታቸው አመራሮችና ሰራተኞች ተሳትፈዋል።
በጉባዔው የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዘዳንት ዶ/ር አነጋግረኝ ጋሻው ሲያደርጉ ቤጌ ምድር በታሪክ በርካታ የጽሑፍ ቅርስ መዛግብትን ጨምሮ እምቅ ሀብት ያለው እንደሆነና የቴዎድሮስን ራዕይ አድርጎ የመጀመሪያውን የመዛግብትና የጽሑፍ ቅርስ ጉባዔ በመጀመሩ ትልቅ ክብር እንደሚሰማውና ዩኒቨርሲቲው ሳይንሳዊ እውቀትን ከሀገር በቀል ዕውቀት ጋር አገናዝቦ እየሰራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል።
የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ይኩኖአምላክ መዝገቡ ኢትዮጵያውያን መዛግብትን የምናስቀምጥበት ታሪክ የቆየ ሲሆን በአንድ በኩል የትዝታ ህዝቦች ስንሆን በአንድ በኩል የትውስታ ጊዜያችንን የተዘናጋንበት ጊዜ ላይ ነው ያለነው በማለት መልዕክት ሲያስተላልፉ ፣የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህል፣ቱሪዝምና ኪነ ጥበባት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ሒሩት ካሳውም በቁልፍ ንግግራቸው ሀገራችን ኢትዮጵያ በስልጣኔ ቀደምት እንደሆነችና የራሷ የፊደል አቆጣጠር ቀን ያላት ስትሆን የጽሑፍ መዛግብቷን በሦሥት መንገድ እያጣች ያለችበት ሁኔታ እንዳለ ተናግረዋል።አንደኛው ከእውቀት ውጪ በሆነና ዝም ብሎ በመጣል ሁለተኛው አሳልፈን በመስጠት ወይም በማዘረፍ ሦሥተኛው ሰንደን ሳናነብ በማስቀመጥ እንደሆነና በበብዙ መንገድ በብዙ ሁኔታ የጽሑፍ ቅርሶቻችንን እየተንከባከብናቸው አይደለም ከዚህ በላይ ደግሞ አንብበን መጠቀም ያለብንን ነገር ተጠቅመን ትውልድና ሀገርን በመገንባት ያላቸውን ሚና አውርደን ያስቀመጥንበትና  የተቀመጥንበትን ጊዜ ስለሆነ ይህንን ካስተዋልን አሁን ግን በደንብ በደንብ አድርገን ስናየው ሁሉም እውቀቱን ተጠቅሞ መጥፎ ዘሮችን የሚያከስም ጥሩ ዘርን የምንዘራበትን ጊዜ መሆን እንዳለበትና የኢትዮጵያ ቤተመዛግብትና ቤተመጻሕፍት አገልግሎት ይህንን ተገንዝቦ እንዲህ ጠቅም ያለው ጉባዔ በመጀመሩ አመስግነዋል።
በመቀጠልም የጉባዔው ዓላማ ላይ ያተኮሩ በርካታ ጥናታዊ ጽሑፎች በኢትዮጵያ ቤተመዛግብትና ቤተመጻሕፍት አገልግሎት ባለሙያ በአቶ አባተ ካሳው፣ከጎንደር ዩኒቨርሲቲ በመ/ር ሰንኮሪስ፣ከደብረ ብርሐን ዩኒቨርሲቲ በመ/ር ደረጀ ሳህለማርያም፣ ከቅርስጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን በዮናስ ይልማ እና ከደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ የታሪክና ቅርስ አስተዳደር መምህር የአለቃ ገ/ሀና ባህል/ጥ/ዳይሬክተር መሠረት ወርቁ የቤጌ ምድር መዛግብት በደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ማቋቋም ለምን እንዳስፈለገ ግንዛቤ የሚሰጡ ጥናቶች ለተሳታፊዎች ሲቀርቡ ከተሳታፊዎችም ጥያቄዎች፣ አሳብ አስተያየት ተሰጥተው ጥናት አቅራቢዎችና አወያዮች ምላሽ በመስጠት ሲጠናቀቅ ሁለተኛ ዙር የመዛግብትና የጽሑፍ ቅርሶች ጉባዔ ባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ለማዘጋጀት በመቀበል ሲጠናቀቅ።
በዕለቱም በዕውቀት የተደራጀው አዲሱ የዩኒቨርሲቲው የመረጃ ግንኙነት ቴክኖሎጂ እና የኢትዮጵያ ቤተመዛግብትና ቤተ መጻሕፍት አገልግሎት የስልጠና ጥናትና ምርምር ዳይሬክቶሬት አዘጋጅነት በተከታታይ የሚሰጠው በሰነድ ስራ አመራርና በመዛግብት አስተዳደር ስልጠና ባለሙያዎችን ቦታው ድረስ በመላክ የተደራጀው በዩኒቨርሲቲው የቤጌ ምድር መዛግብት ክምችትና አገልግሎት ማዕከል በዕለቱ ሲመረቁ ለአለቃ ገ/ሀና የቤጌ ምድር መዛግብትና ክምችትና አገልግሎት ማዕከል ከአገልግሎቱ ዲጂታል ጥንታዊ ጽሑፍ አርድ ዲስክ፣በዩኔስኮ የተመዘገበው የአፄ ቴዎድሮስ ደብዳቤ በፍሬም በማድረግ ሲበረከት ከተለያዩ ወረዳዎችና ከደብረ ታቦር ከተማ ተውጣተው መሰረታዊ ሙያ ሳይንስ እና የቤተ መጻሕፍት ሙያ ስልጠና ለሰለጠኑ በአጠቃላይ ሰላሳ ሰባት ሰልጣኞች የምስክር ወረቀት ተበርክቷል።
በዕለቱም ለአራት የሕዝብ ቤተ መጻሕፍት ቤቶች፣ለአራት የትምህርት ቤት ቤተ መጻሕፍትና ለደብረ ታቦር ከተማ ማረሚያ ቤት በቁጥር 5278 መጽሐፍት በብር 1,191,566 የፈጁ መበርከታቸው ተጠቁሟል።

Share this Post